የም ዞን
የየም ዞን ታሪካዊ መስህብ
ጥንታዊየአንገሪ ቤተ መንግሥት
የየም ብሔረሰብ የራሱን የአስተዳደር መዋቅር መስርቶ በንጉሡ /ታቶ/ይተዳደር ነበር፡፡ ህዝቡን ሶስትሥርወ መንግሥታት ተፈራርቀው አስተዳድረውታል፡፡ የመጀመሪያው የጋማሥርወ መንግሥት ማዕከላዊ መቀመጫውን ዝማር-ማ /ኦያ አካባቢ/ በሚባል ስፍራ በማድረግ፣ሁለተኛው የጌሜሎ ሥርወ መንግሥት የሥርወ መንግሥቱን ማዕከላዊ መቀመጫ ካንፎቻ/ፎፋ መድኃኒዓለም ቤ/ክርስቲያን በስተጀርባ/ እና የሞዋሥርወ መንግሥት ማዕከላዊ መቀመጫውን አንገሪ በማድረግ ብሔረሰቡን አስተዳድረዋል፡፡ የአንገሪ ቤተ መንግሥት ከ13ኛው ክፍለ ዘመን 2ኛ አጋማሽ አንስቶ የየም ግዛት በማዕከላዊ ግዛት ውስጥ እስኪገባ ድረስ የሞዋ ሥርወ መንግሥት መቀመጫና መናገሻ በመሆን አገልግሏል፡፡እስከ 1894 እንደ አውሮፓውያን ዘመን አቆጣጠር የየምን ብሔረሰብ የመሩ አባቦጊቦ/የባህል ስማቸው ጎሳስኖ/ ሲሆኑ ከሳቸው በመቀጠል ልጃቸው የሆኑት ጌራኖ/ፊታውራሪ ገ/መድህን/ ብሐረሰቡን በባህላዊ አስተዳደር መርተዋል፡፡ እኚህ ንጉስ ዘመናዊ ትምርትን በ1938 ዓ.ም አፄ አምደጽዮን አሁን የፎፋ ሁለተኛና መሰናዶ ት/ቤት የሚባለውን እና በ1888 ዓ.ም የፎፋ ደብረ መድኃኒት መድኃኒዓለምን ቤተ ክርስቲያንን ከዳግማዊ አፄ ምኒሊክ ዘንድ በማምጣት ተክለዋል፡፡በመሆኑም ህዝቡ ኬምኒ/ የሚል ስም የሰጣቸው ሲሆን ትርጉሙም ዓይናችን ማለት ነው፡፡
ጥንት ቤተ መንግስተቱ ዙሪያው በሦስት አጥር የታጠረ እንደነበር የብሄረሰቡ አዛውንቶች ሲያስረዱ አሁን ላይ ቤተመንግስቱ አቅራቢያ የሚገኝው አንዱ አጥር ብቻ ይገኛል፡፡ በዚህ በቤተ መንግስቱ ቅጥር ግቢ ውስጥም ቁጥራቸው 12 የሚደርሱ የተለያየ አገልግሎት የሚሰጡ ቤቶች እንደነበሩ ከነዚህ ውስጥም የምግብ አዳራሽ፣ሥጋ ቤት፣ጠላ ቤት፣ጠጅቤት፣እስርቤት እና የንጉሱ ማደሪያቤቶች ተጠቃሽ ሲሆኑ ለዚህም ማሳያ የአንዳንዶቹ ቤቶች ምሶሶ እስካሁን ድረስ በስፍራው ይገኛል፡፡
ቤተ መንግሥቱ ከዞኑ ከተማ ሳጃ 27.8 ኪሎ ሜትር በደቡባዊ ምስራቅ አቅጣጫ በጎሩምና አንገሪ ቀበሌ ሲገኝ ዛሬም ድረስ በስፍራው የሚገኙት በርካታ ታሪካዊ ሥነ-ሥርዓትና ክንዋኔዎች የተፈፀመባቸው ቦታዎች እንዲሁም ግርማ ሞገስ ያላቸው እድሜን ያስቆጠሩ አገር በቀል ዛፎች ለጥንታዊነቱ ህያው ምስክሮች ናቸው፡፡
ቤተ መንግሥቱ ሦስት በሮች ሲኖሩት የመጀመሪያው ለጉዳይ ወደ ንጉሡ የሚመጡ እንግዶች የሚገቡበት በር፣ ሁለተኛው ንጉሡ ከመኖሪያ ቤታቸው ወደ ቤተ-መንግሥቱ የሚገቡበትና ሦስተኛው ንጉሡ በቤተ-መንግሥቱ ቅጥር ወደሚገኘው ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የሚሄዱበት በር ሲሆን በዚህ ስፍራ የነበረው የጊዮርጊስ ታቦት በአሁኑ ጊዜ ማፎ አካባቢ ይገኛል፡፡ የቤቱ አሰራርን ስንመለከት እያንዳንዱ ትርጉም ያለው ሲሆን ምሶሶው ንጉሱን ይወከወላል፣ወጋግራዎቹ/ቶሬ/ የጎሳ መሪዎችን ይወክላሉ፣ሌሎች የጣሪው ክፍል ህዝቡን ሲወክሉ ከምሶሶው አናት ላይ የተቀመጠው መስቀል መጀመሪያ ክርስትናን መቀበላቸውን ያሳል፡፡
መነሻችንን ከዞኑ ርዕሰ ከተማ ሣጃ ካደረግን 27.8 ኪ.ሎ ሜትር እንደ ተጓዝን ወደ ቤተ-መንግስቱ የሚያደርሰውን መገንጠያ መንገድ እናገኛለን፡፡ ከመገንጠያው አንድ ኪ.ሎ ሜትር እንደተጓዝን ታሪካዊ ድርጊት የተፈፀመበትን ቦታ ያገኛሉ፡፡ የቦታው ስም «ቱም ቱም»ይባላል፡፡ትርጉሙንም ያገኘው በብሄረሰቡ ቋንቋ የምሳ ቱማ/ደንብ/ ከሚለው እና ከቤተ መንግስቱ ወደ እዚህ ስፍራ ውስጥ ለውስጥ የመጣ ዋሻ አለ ስለሚባል እዚህ ስፍራ ላይ ሲረገጥ ቱም ቱም ብሎ ከሚያሰማው ድምጽ ሲሆን «ቱም ቱም ማለት የሥርዓት ወይም የደንብ መወሰኛና መቋጫ ቦታ ማለት ነው፡፡ ጥንት በነገስታቱ ጊዜ የሚወጣው ደንብ ፤የዳር ድንበር ጉዳይ፤ ወረራና ጦርነት እንዲሁም የውጭ ግንኙነት ጉዳይ በመሳሰሉት አጠቃላይ ነገሮች ላይ የየጎሣ ተወካዮች «አስተሰር/ ከተለያዩ ጎሳዎች የተወከሉ 12 ሰዎች / ናንተሰር/ ከሁሉም ጎሳዎች የተወከሉ ሰዎች/ እና ቱምተሰር /የህግ አውጪ/ » አማካይነት ጉባኤ ተደርጎ ውሳኔ ተሰጥቶ እዚያው ቦታ ላይ በንጉስ ፀድቆ ወደ ተግባር እንዲገባ ይደረጋል፡፡ እስከ አሁንም በቦታው ያሉ ቅርሶች እማኞች ሆነው ይገኛሉ ፡፡ እነዚህም እድሜ ጠገብ የዝግባ ዛፎች፤ የንጉሱ መቀመጫ ጠፍጣፋ ድንጋይ ምስክሮች ናቸው፡፡ከቱምቱም ትንሽ ወረድ እንዳልን በግምት አንድ መቶ ሜትር እንደተጓዝን የቤተ-መንግስቱን የመጀመሪያ በር ኬላ እናገኛለን ፡፡ ስሙም « ቦቾ» ይባላል፡፡ በዚህ ኬላ ላይ የደረሰ ሰው ለምን የት እንደሚሄድ በቦታው ባሉት ዘበኞች ይጠየቃል ፡፡ ወደ ንጉሱም ዘንድ ጉዳይ ካለው መልዕክተኛ ተልኮ የመግቢያ ፍቃድ ከተሰጠ ወይም ወደ ውስጥ ይግባ የሚል መልዕክት ከደረሳቸው በኃላ ወደ ቤተ-መንግስቱ እንዲገባ ይደረጋል፡፡ ሁለቱ ዘበኞች እያረፉ የሚጠብቁበት ሁለት ጠፍጣፋ ድንጋዮችን እናገኛለን፡፡ ከዚያም ቁልቁለቱን ተጉዘን እንደጨረስን አቦር የሚባል ቦታ እናገኛለን፡፡ አቦር የቅጣት ቦታ ሲሆን የቅጣቱ አይነት አቦር በልሱ ይባላል፡፡ በዚህ ቦታ የሚቀጡ ሰዎች የሰውን ልጅ የደፈሩ ፣የሰውን ሚስት ያማገጡ ሰዎች እጀና እግራቸው በችካል ተወጥሮ የሚቀጡበት የቅጣት አይነት ነው፡፡ የቤተ- መንግስቱ ዙሪያ በርካታ ታሪካዊ ድርጊቶች የተፈፀመባቸው ስለመሆናቸው ታሪካዊ አሻራዎችን እንመለከታለን፡፡

ቾክቾከር፡- በወቅቱ ቤተ መንግስት አካባቢ ደም እንዲፈስ ስለማይፈቀድ ምክንያቱም የተከበረ ቦታ ስለሆነ የቤተ መንግስቱ ሰዎች ፀጉራቸውን የሚላጩበት ስፍራ ነው፡፡ በወቅቱም ይላጩ የነበረው በባልጩት ስለነበረ ሲላጩ ከሚያሰማው ድምጽ ተነስቶ ስሜው እንደተሰጠ ይነገራል፡፡
ፌታርኒኪ፡-የጎሳ ተወካዮች/ አስተሰሮች/ በተለያዩ ጉዳዮች መክረው የመጨረሻ ውሳኔ የሚያስተላልፉበት ስፍራ ነው ፡፡
ዓላማ ካሻ፡- በዓላትን የሚያከብሩበትና የእንግዳ ማረፊያ እና የቤተ-መንግስቱ ሰዎች የሚዝናኑበት ቦታ ስም ነው፡፡
ዳጋ አፋኣ፡-የቤተ-መንግስቱ ሰዎች መዝናኛ እና የውሃ ዋና መለማመጃ ቦታ ነው
መች መኖኪ፡- ንጉሱ ሁለተኛ ሚስት ሲያገባ የምትኖርበት ቤት ቦታ ስም ነው፡፡
አንገር አፋኣ፡- የቤተ-መንግስቱ ሰፊ የእንሰት ማሳ ቦታ ነው፡፡
ኡሳሱኒሲ፡- ቆጮ ተፍቆ የሚከማችበትና እና ለምግብ ቆጮ የሚዘጋጀበት ቦታ ስም ነው፡፡
ጋርባሱኒስ፡-የጋማ ከብት ማጎሪያ ቦታ
ወጀላ፡- የቤተ-መንግስቱ አገልጋዮች የሚኖሩበት ቦታ ስም ነው ለምሳሌ መልእክት የሚያደርሱ፣ለቤተ ክርስቲያን የሚያገለግሉ ቅዱሳት መጽሐፍት የብራና ቀለም አዘጋጀተው የሚጽፉ ደብተራዎች ፣ የንጉሱ አማካሪዎች እና ሌሎቹም የሚኖሩበት ስፋራ ስም ነው ፡፡
ጋማልሲ፡-የእንሰት ችግኞች ማፊያ ቦታ ነው/በብሄረሰቡ ቋንቋ በየምሳ ጉፋ ፋሽተና ዳ / ከቤተ መንግስቱ በስተ ምስራቅ አቅጣጫ ይገኛል፡፡
ኦቱምሲ፡-የንጉሱ የወተት ላሞች ማደሪያ ቤት ያለበትና የእንሰት ተክል ስፍራ ነው
ሜውሹኬር፡- በጥንት ጊዜ የዱር እንስሳት ከጫካ ወደ ሰዎች መንደር በመምጣት ሰዎችና የቤት እንስሳት ላይ ጉዳት ያደርሱ ነበር ፡፡ በመሆኑም እነዚህ ከጫካ ወደ ሰው መንደር በመምታት ጉዳት ከሚያደርሱ የዱር እንስሳት መካከል አንዱ ነብር ነበር፡፡ በወቅቱ ይህንን ነብር የገደለ ሰው ከንጉሱ የጀግንነት ማረጉን ከንጉሱ ለማግኘት ነብሩን አምጥቶ ቆዳ የሚገፍበት ቦታ ስም ነው፡፡
አንገር ፎቻራ፡- የቤተ መንግስቱ ደጃፍ ማለት ነው፡፡
አውቱንሲ ፡- ከቤተ መንግስቱ በስተ ሰሜን አቅጣጫ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤ/ክርስቲያን የነበረበት ስፍራ ስም ነው
ሱቶሲ ፡- መለያ ማለት ሲሆን የቤተ መንግስቱ ሰዎች እና ሌሎች ነዋሪዎች የሚለዩበት ቦታ ስም ነው፡፡
ቤተ-መንግስቱ የተመሰረተበት ዘመን በግምት ከ13ኛው ክፍለ ዘመን 2ኛ አጋማሽ ወዲህ መሆኑን መረጃዎች ይገልፃሉ፡፡ በተጨማሪም እጅግ ጥንታዊ ስለመሆኑ የ ሚመሰክሩ መረጃዎች ይታያሉ እነዚህም ፡- የቤተ-መንግስቱን ቤትና አጥር ለማደስ ሲባል የመሬት ቁፋሮ ሲደረግ ጥንታዊ የሸክላ ዕቃ መገኘት ፣ የቤተ መንግስት ሰዎች መጫወቻ የነበረው የድንጋይ ገበጣ ጉድጓዶች በድንጋዩ ውስጣዊ እንቅስቃሴ ምክንያት ጉድጓዶች የተሞሉ መሆኑ፣ ቤቶቹ ረዥም ዘመን በማገልገላቸው አርጅተው መውደቅና የአጥር ፍርስራሽ ጭምር መገኘት፣ በጣም ያረጁ ዕድሜ ጠገብ ሀገር በቀል ዛፎች በብዛት ያሉ መሆኑ፣ የተለያዩ አገልግሎት መስጫ ተብሎ የተሰሩ የተካቡ የድንጋይ ካብ መድረኮች በብዛት መገኘት ፣ወዘተ ….ናቸው፡፡
የቤተ መንግስቱ ቦታ በዋናነት ከጥንት ጊዜ ጀምሮ የተለያዩ ነገስታት በመፈራረቅ ሲያስተዳድሩ የነበሩበት መናገሻ ሆኖ ስያገለግል ቆይቷል፡፡ በተለይም የሞዋ ሥርወ መንግስት ከ13ኛው ክፍለ ዘመን 2ኛው አጋማሽ ጀምሮ ሥልጣን ተረክቦ ሲያስተዳድር ነበር፡፡
በአንገሪ ቤተ-መንግስት የነገሱ የሞዋ ስርወ መንግስት ንጉሳን ስም ዝርዝር 12 ሲሆኑ እነርሱም፡-
1. ባላም (ባለወልድ) 7. ኖዲኖ
2. አዛግኖ 8. ዛርማዲኖ
3. ቶኪኖ 9. ዲጋምኖ
4. ሰልባብኖ 10. አዱሎኖ
5. ማውዲኒኖ 11. አባ ቦጊቦ /የባህል ስማቸው /ጎሳስኖ/
6. ኮከኖ 12. ጌራኖ (ፊት አውራሪ ገ/መድህን) ናቸው፡፡
እስከ 1894 እንደ አውሮፓውያን ዘመን አቆጣጠር ድረስ የየም ብሔረሰብ ያስተዳደሩ/የመሩ/የሞዋ ስርወ መንግስት ንጉስ የባህል ሥማቸው ጎሣስኖ ዋና ስማቸው አባቦጊቦ ዘመነ መንግስት ድረስ የአንገሪ ቤተ-መንግስት የታወቀና ገናና አከባቢ ሆኖ ነበር፡፡ በኋላም ልጃቸው የሆኑት ጌራኖ/ፊታውራሪ ገ/መድህን ቦጊቦ/ በቦታቸው ተተክተው መቀመጫቸውን በዚሁ ቤተ-መንግስት በማድረግ ብሔረሰቡን በባህላዊ አስተዳደር መርተዋል፡፡